Obadiah (Amharic)

Obadiah (Amharic)

1

1:1b.OBA.001.001የአብድዩ ራእይ። ጌታ እግዚአብሔር ስለ ኤዶምያስ እንዲህ ይላል። ከእግዚአብሔር ዘንድ ወሬ ሰምተናል፤ መልእክተኛ ወደ አሕዛብ ተልኮ። ተነሡ፥ በላይዋም በሰልፍ እንነሣ ብሎአል።

1:2b.OBA.001.002እነሆ፥ በአሕዛብ ዘንድ ታናሽ አድርጌሃለሁ፤ አንተ እጅግ ተንቀሃል።

1:3b.OBA.001.003በተሰነጠቀ ዓለት ውስጥ የምትኖር፥ ማደሪያህንም ከፍ ከፍ ያደረግህ፥ በልብህም። ወደ ምድር የሚያወርደኝ ማን ነው? የምትል አንተ ሆይ፥ የልብህ ትዕቢት አታልሎሃል።

1:4b.OBA.001.004እንደ ንስር መጥቀህ ብትወጣ፥ ቤትህም በከዋክብት መካከል ቢሆን፥ ከዚያ አወርድሃለሁ፥ ይላል እግዚአብሔር።

1:5b.OBA.001.005ሌቦች ቢመጡብህ ወይም ወንበዴዎች በሌሊት ቢመጡ፥ የሚበቃቸውን የሚሰርቁ አይደሉምን? ወይንንም የሚቈርጡ ወደ አንተ ቢመጡ ቃርሚያ አያስቀሩምን?

1:6b.OBA.001.006አንተ ግን ምንኛ ጠፋህ! ዔሳው ምንኛ ተመረመረ! የተሸሸገበት ነገር ምንኛ ተፈለገ!

1:7b.OBA.001.007የተማማልሃቸው ሰዎች ሁሉ ወደ ዳርቻህ ሰደዱህ፤ የታመንሃቸው ሰዎች አታለሉህ፥ አሸነፉህም፤ በበታችህም አሽክላ ዘረጉብህ፥ እነርሱም ማስተዋል የላቸውም።

1:8b.OBA.001.008በዚያ ቀን ከኤዶምያስ ጥበበኞችን፥ ከዔሳውም ተራራ ማስተዋልን አላጠፋምን? ይላል እግዚአብሔር።

1:9b.OBA.001.009ቴማን ሆይ፥ ሰዎች ሁሉ ከዔሳው ተራራ በመገደል ይጠፉ ዘንድ ኃያላንህ ይደነግጣሉ።

1:10b.OBA.001.010በወንድምህ በያዕቆብ ላይ ስለ ተደረገ ግፍ እፍረት ይከድንሃል፥ ለዘላለምም ትጠፋለህ።

1:11b.OBA.001.011በፊቱ አንጻር በቆምህ ቀን፥ አሕዛብ ጭፍራውን በማረኩበት፥ እንግዶችም በበሩ በገቡበት፥ በኢየሩሳሌምም ዕጣ በተጣጣሉበት ቀን አንተ ደግሞ ከእነርሱ እንደ አንዱ ነበርህ።

1:12b.OBA.001.012ነገር ግን በመከራው ቀን ወንድምህን ትመለከት ዘንድ፥ በጥፋታቸውም ቀን በይሁዳ ልጆች ላይ ደስ ይልህ ዘንድ፥ በጭንቀትም ቀን በትዕቢት ትናገር ዘንድ አይገባህም ነበር።

1:13b.OBA.001.013በጥፋታቸውም ቀን በሕዝቤ በር ትገባ ዘንድ፥ በጥፋታቸውም ቀን መከራቸውን ትመለከት ዘንድ፥ በጥፋታቸውም ቀን በሀብታቸው ላይ እጅህን ትዘረጋ ዘንድ አይገባህም ነበር።

1:14b.OBA.001.014የሸሹትንም ለመግደል በመንታ መንገድ ላይ ትቆም ዘንድ፥ በጭንቀትም ቀን ከእርሱ የቀሩትን አሳልፈህ ትሰጥ ዘንድ አይገባህም ነበር።

1:15b.OBA.001.015የእግዚአብሔር ቀን በአሕዛብ ሁሉ ላይ ቀርቦአልና፤ አንተ እንዳደረግኸው እንዲሁ ይደረግብሃል፥ ፍዳህም በራስህ ላይ ይመለሳል።

1:16b.OBA.001.016በቅዱስ ተራራዬ ላይ እንደ ጠጣችሁ እንዲሁ አሕዛብ ሁሉ ዘወትር ይጠጣሉ፤ አዎን ይጠጣሉ፥ ይጨልጡማል፥ እንዳልሆኑም ይሆናሉ።

1:17b.OBA.001.017ነገር ግን በጽዮን ተራራ ላይ የሚያመልጡ ይሆናሉ፥ እርሱም ቅዱስ ይሆናል፤ የያዕቆብም ቤት ሰዎች ርስታቸውን ይወርሳሉ።

1:18b.OBA.001.018እግዚአብሔርም ተናግሮአልና የያዕቆብ ቤት እሳት፥ የዮሴፍ ቤት ነበልባልም፥ የዔሳው ቤት ገለባ ይሆናሉ፤ እነርሱንም ያቃጥሉአቸዋል ይበሉአቸውማል፤ ከዔሳውም ቤት ቅሬታ የለውም።

1:19b.OBA.001.019የደቡብም ሰዎች የዔሳውን ተራራ፥ የቈላውም ሰዎች ፍልስጥዔማውያንን ይወርሳሉ፤ የኤፍሬምንም አገር የሰማርያንም አገር ይወርሳሉ፤ ብንያምም ገለዓድን ይወርሳል።

1:20b.OBA.001.020ይህም የእስራኤል ልጆች የጭፍራቸው ምርኮ የከነዓንን ስፍራ ሁሉ እስከ ሰራጵታ ድረስ ይወርሳል፤ በስፋራድም የሚኖሩ የኢየሩሳሌም ምርኮኞች የደቡብን ከተሞች ይወርሳሉ።

1:21b.OBA.001.021በዔሳውም ተራራ ላይ ይፈርዱ ዘንድ አዳኞች ወደ ጽዮን ተራራ ላይ ይወጣሉ፤ መንግሥቱም ለእግዚአብሔር ይሆናል።


Holder of rights
Multilingual Bible Corpus

Citation Suggestion for this Object
TextGrid Repository (2025). Amharic Collection. Obadiah (Amharic). Obadiah (Amharic). Multilingual Parallel Bible Corpus. Multilingual Bible Corpus. https://hdl.handle.net/21.11113/0000-0016-8A6D-3